የተፈጥሮና ቀመር ሳይንስ ኮሌጅ የመጀመሪያውን ሴሚናር “The Nexus between Science and Education” በሚል ርዕስ የሳይንስ ትምህርት ላይ ትኩረት በማድረግ ያዘጋጀውን አውደ ጥናት በንግግር የከፈቱት የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶ/ር ብርሃነመስቀል ጠና እንደገለፁት፣ ኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሻገር የተለያዩ የስልጠና እና የግንዛቤ ማስጨበጫ መርሐግብሮች እየተከናወኑ ናቸው፡፡ ከነዚህም መርሐግብሮች መካከል በተለያዩ ጊዚያት የተከናወኑ ልዩ ልዩ ጥናቶች፣ በጥናቶቹ ላይ የተካሄዱ የምክረ ሐሳብ ውይይቶች በአብነት የሚጠቀሱ ሲሆን የሳይንስ ትምህርትን ሚና በማስመልክት የተዘጋጀው የዛሬው መድረክም የዩኒቨርሲቲውን አጠቃላይ ሂደት ወደ ትልቅ ደረጃ ለማሻሸገር በእጅጉ ጠቃሚ መድረክ መሆኑን ፕሬዝዳንቱ አመልክተዋል፡፡
መምህር አንድም አስተማሪ ነው፤ አንድም ተማሪ በመሆኑ ትምህርት ሁሌም አዲስ ነው ያሉት ዶ/ር ብርሃነመስቀል፣ ዩኒቨርሲቲውን ወደ ላቀ ደረጃ ለማድረስ በሚደረገው ጥረት ውስጥም መምህራን ንቁ ተሳታፊ በመሆን መወያየት እና የተሻለ ሃሳብ ማፍለቅ እና መያዝ የሚጠበቅባቸው ስለሆነ ከዚህ አውደ ጥናት በተጨማሪም በየጊዜው የሚገኙ ሃሳቦችንም የጋራ ለማድረግ እንዲቻል የዩኒቨርሲቲው መምህራን ስልጠና እንደሚወስዱም ተናግረዋል፡፡
በአውደ ጥናቱ ላይ ሁለት ጥናታዊ ጽሑፎች በዶ/ር ተመቸኝ እንግዳ እና በዶ/ር ካሳ ሚካኤል የቀረቡ ሲሆን የሳይንስ ትምህርት ለሳይንስና ቴክኖሎጂ፣ ለኢኮኖሚ፣ ለተፈጥሮ ሳይንስ፣ ለግብርና እና ለሌሎች መስኮች መሰረት በመሆኑ አዲሱን ትውልድ በሳይንስ መስክ ብቁ እና ሥራ ፈጣሪ ለማድረግ ከሥርዓተ ትምህርት ቀረፃ ጀምሮ፣ የዩኒቨርሲቲው የትምህርት ዓይነት እና ይዘት ሀገር ዓቀፍ እና ዓለም ዓቀፍ ገፅታ እንዲኖረው ለማስቻል በኮተቤ ትምህርት ዩኒቨርሲቲ ውስጥ የሚገኙ የትምህርት ክፍሎች እና መምህራን በህብረት መስራት እና የዩኒቨርሲቲውን አወቃቀርም ሆነ ዓላማ ተግባራዊ ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው ተገልጿል፡፡
የማኅበረሰብ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር የሆኑት ዶ/ር በሊና ተርፋሳ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት የዩኒቨርሲቲው አወቃቀር እና አካሄድ በቀጣይ ምን መልክ ሊኒኖረው እንደሚገባ መሠረታዊ ግንዛቤና እውቀት ያገኘን በመሆኑ በዚህ መልክ እየተሰራ ስለመሆኑ አውደ ጥናቱ የዩኒቨርሲቲውን ቀጣይ ሂደት ለመገምገም ያስችለናል ያሉ ሲሆን የፋካልቲው ዲን ዶ/ር ማስረሻ አማረ ደግሞ፣ መድረኩ ጠቃሚ በመሆኑ ይህን መሰሉ አውደ ጥናት በቀጣይም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመልክተዋል፡፡
የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት