ሰኔ 06/2014 ዓ.ም
ኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ የአካል ጉዳተኛ ለሆነችው ተማሪ ሠላማዊት ጎርፉ አስፈላጊ የሆኑ ቁሳቁሶችን ሰኔ 06/2014 ዓ.ም ድጋፍ አድርጓል፡፡
የኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት የተከበሩ ዶክተር ብርሃነመስቀል ጠና ስጦታውን በሰጡበት ወቅት እንዳሉት፤ ተማሪዋ ስትጠቀምበት የነበረው ዊልቸር በጣም ከማርጀቱ የተነሳ ለበርካታ ጉዳቶች ዳርገዋት እንደነበር ገልፀው፤ የዩኒቨርሲቲው የአስተዳደር ካውንስል በወሰነው መሠረት ተማሪዋ ካለባት ተደራራቢ የሆኑ ችግሮች አንፃር የዊልቸር እንዲሁም የሳምሰንግ ታብሌት ስልክ ተገዝቶ በድጋፍ የተበረከተላት መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ተማሪ ሠላማዊት ጎርፉ እግሮቿንና እጆቿን እንደፈለገች ያለማንቀሳቀስ ችግር፤ እንዲሁም የመናገር ችግር ያለባት ብትሆንም ይህንን ሁሉ ተደራራቢ ጉዳቶች ችላ ትምህርቷን በጥሩ ሁኔታ እየተከታተለች በመሆኑ ስጦታው ይገባታል ሲሉ ፕሬዝዳንቱ ገልፀዋል፡፡
ስጦታው የተበረከተላት ተማሪ ሠላማዊት ጎርፉ በጂኦግራፊ ትምህርት ክፍል የመደበኛው መርሐ ግብር የመጀመሪያ ዲግሪ የ3ተኛ ዓመት ተማሪ መሆንዋን ለማወቅ ተችሏል፡፡