ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ “ለኢትዮጵያ ልዕልና፣ የምሁራን ሚና” ሚል ሀሳብ በኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ እና በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ህዳር 26/2015 ዓ.ም በኃይሌ ግራንድ ሆቴል በተካሄደው የምሁራን መድረክ ላይ ተገኝተው በሰጡት ገለፃ፣ ለሁሉም የምትመች የጋራ የሆነች ኢትዮጵያን ለመፍጠር የምሁራን ሚና ከፍተኛ ነው፡፡
ኢትዮጵያ ለመበልፀግ ዕድል ያላት ሀገር ናት ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ሀገሪቷ በቂ የሰው ኃይል፣ ሰፊ ያልታረሰ ድንግል መሬት፣ የተፈጥሮ ሃብት እና ማህበረዊ ካፒታል ያላት በመሆኗ ብልፅግናዋን ለማረጋገጥ ምሁራን የፖሊሲ ግብዓቶችንና አሻጋሪ ምክረ-ሃሳቦችን በማቅረብና የውይይት ባህልን በማዳበር ከመንደር አስተሳሰብ የተሸገረ ሀገራዊ የሀሳብ ልዕልና እንዲሰፍን በማድረግ ረገድ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡
በመድረኩ የመክፈቻ ንግግራቸው የኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ብርሃነመስቀል ጠና፤ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በመማር ማስተማር ሀገር ተረካቢ ትውልድ ከመቅረፅ ባሻገር የሚሰሯቸውን ጥናትና ምርምሮችን መሠረት በማድረግ አካባቢያዊ እና ቀጠናዊ ችግሮቻችንን በመፍታት ረገድ ምሁራን ከፍተኛ ሚና እንዳላቸው ገልፀዋል፡፡ ሀገራዊ ተልዕኳችንን ከግብ ለማድረስ ተግተን መስራት ይጠበቅብናል ያሉት ፕሬዝዳንቱ፣ ተልዕኳችንም ሲደመር ግቡ አንዲት እናት ሀገርን መገንባት እንዲሁም ብልፅግናችንን እውን ማድረግ ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡
በመድረኩ ላይ ዶ/ር ሳሙኤል ተፈራ እና ዶ/ር ደቻሳ አበበ የዕለቱ ርዕሰ-ጉዳዮችን አስመልክተው የውይይት መነሻ ሀሳቦችን ያቀረቡ ሲሆን ተሳታፊ ምሁራንም የቀረቡትን ሀሳቦች በውይይት አዳብረዋል፡፡
በውይይቱ መዝጊያ ላይ የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ደረጀ እንግዳ፣ በመድረክ ላይ የተነሱት ሀሳቦች በተግባር ላይ እንዲውሉ ሁሉም ምሁራን የበኩላቸውን አስተዋፅዖ እንዲያበረክቱ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
በዕለቱ የምክክር መድረክ ላይ ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች፣ የምርምር ተቋማትና ከባለድርሻ መ/ቤት የተወጣጡ ምሁራን መሳተፋቸውን ለማዋቅ ተችሏል፡፡
የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት